ሰኔ 7 ቀን 2014 ዓ.ም. በጋምቤላ ከተማ፣ ጋምቤላ ክልል ከጠዋት እስከ ምሽት የቀጠለ ግጭት እና የፀጥታ እና የደኅንነት ችግርን ተከትሎ ለአንድ ቀን የከተማዋ የመንግሥት አገልግሎቶች፣ የንግድ እንቅስቃሴዎች እና ሌሎችም አገልግሎቶች ተቋርጠው መዋላቸው ይታወሳል። ጥቃቱ በኦሮሞ ነጻነት ግንባር (በተለምዶ ኦነግ ሸኔ) እና በጋምቤላ ነጻነት ግንባር ታጣቂዎች የተከፈተ እንደነበር እና ክስተቱ በቁጥጥር ሥር እንደዋለ የክልሉ መንግሥት አሳውቋል። በዕለቱ የመንግሥት የፀጥታ አካላት በወሰዱት እርምጃ የከተማዋ ፀጥታ የተረጋጋ እና በአሁኑ ወቅት የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት በከተማው የሚገኝ ቢሆንም እስከ አሁንም ድረስ የተሟላ መረጋጋት አለመስፈኑን፣ የነዋሪዎች የእለት ተዕለት እንቅስቃሴ ሙሉ በሙሉ አለመጀመሩን፣ እንዲሁም በተለይም የንግድ አካባቢዎችን ጨምሮ በአንዳንድ ስፍራዎች ዘረፋ እንደተፈጸመ ነዋሪዎች ለኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) አስረድተዋል። 

በተጨማሪም ከሰኔ 8 ቀን 2014 ዓ.ም. ጀምሮ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች (በክልሉ ልዩ ኃይል እና መደበኛ ፖሊስ) በተወሰዱ የኃይል እርምጃዎች ምክንያት ነዋሪዎች ለተለያዩ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች እየተጋለጡ መሆናቸውን እና ከሕግ ውጭ ግድያ ስለመፈጸሙ ለኢሰመኮ መረጃዎች እየደረሱት ይገኛል። በተለይም በጥቃቱ ተሳትፈዋል ወይም ተባብረዋል ተብለው በተጠረጠሩ ግለሰቦች ላይ ቤት ለቤት በመሄድ ጭምር ግድያዎች እንደተፈጸሙ ኢሰመኮ ከምስክሮችና የተንቀሳቃሽ ምስል ማስረጃዎች ጭምር ካሰባሰባቸው መረጃዎች ለመረዳት ችሏል። 

የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ዳንኤል በቀለ (ዶ/ር) የሰዎችን ደኅንነትና የከተማዋን ሰላም ማረጋገጥ ቀዳሚው ተግባር መሆኑን አስታውሰው፣ ይህንን ተግባራዊ ለማድረግ የሚወሰዱ እርምጃዎች በሙሉ የሰብአዊ መብቶችን መርሆች ሊከተሉ እንደሚገባ አሳስበዋል። በተለይም የፀጥታ ኃይሎች ሕይወት ሊያጠፋ ከሚችል ተመጣጣኝ ያልሆነ የኃይል እርምጃ እንዲቆጠቡና በፀጥታ ኃይሎች የተወሰዱ ሕገ ወጥ ተግባራት ላይ በአስቸኳይ ማጣራት ተደርጎ ተጠያቂነት እንዲረጋገጥ አሳስበዋል።